Friday, February 16, 2018

ለቪኦኤ እንግዶች፤ ብርሃኑ፤ ገብሩ፤ መረራና ልደቱ ጌታቸው ረዳ (ኢትዮ ሰማይ አዘጋጅ)

ለቪኦኤ እንግዶች ብርሃኑ ገብሩ መረራና ልደቱ
ጌታቸው ረዳ
(ኢትዮ ሰማይ አዘጋጅ)
ትናንት ያደመጥነው የኃይለማርያም ደሳለኝ ከሥልጣን መውረድ አስመልክቶ የ4ት ታዋቂ የፖለቲካ ድርጅት መሪዎች ባደረጉት ውይይት ላይ አንድ ልበል። በፌስ ቡክ  በተደረገው የስልክ ውይይት ከአድማጮችና ከአዘጋጆቹ  የቀረቡ በርካታ ጥያቄዎች ተቃዋሚዎቹ በቂ መልስ አልሰጡም። አወያይዎች ትርጉሙ ባልገባኝ ምክንያት ለብርሃኑ ነጋ ከሌሎቹ በበለጠ የተለጠጠ የመናገር ዕድል በመስጠት የሌሎቹን መልስ በበቂ እንዳናደምጥ ማድረጋቸው አድላዊ የሆነ የዘወትር ልማዳቸውን መከተላቸው ዛሬም እየደገሙት ነው። ያለ ብርሃኑ ነጋ ሌላ ኢትዮጵያዊ ተቃዋሚ የማያውቁ ምስኪኖቹ  የቪ ኦ ኤ አማርኛው ክፍል አዘጋጆች ይህን የሚያደርጉት ሆን ብለው  በሻዕቢያ የሚረዳው ግንቦት 7 የተባለ ተቀጣሪ ቡድን በኢትዮጵያ ሕዝብ አድማጮች ጆሮ አንዲገባ በማስተዋወቁ ረገድ ምስኪኑ ኢትዮጵያ ሕዝብ ለካ ተዋጊ ሃይል አለን ብሎ አጉል ተስፋ እንዲጥልበት ልዩ ማስታወቂያ (አድቨርታይዝ) እየሠሩለት መሆኑን እየታዘብን ነው። ትችቴ እንደሚከተለው ነው።

ውይይቱን ለማድመጥ ይህንን ማስፈንጠሪያ ይጠቀሙ፡
Ethiopia: Dr Berhanu Nega, Dr Merera Gudina, Lidet Ayalew, Gebru Asrat PM Hailemariam Resignation

ልደቱ ባለው የተበላሸ የፖለቲካ አቁዋሙ የሚያራምደው መስምር የማልወድለት ብሆንም፤ ያ እንዳለ ሆኖ በትክክል እንዳለው በእንግድነት የተጋበዙት “ተቃዋሚዎች” <<እራሱን ቸምሮ ለተጠየቁት ጥያቄዎች መልስ ማግኘት እንዳልቻሉ  ያሳያል>> ያለውን በትክክል የኔን መስመር ማጠናከሩ ልደቱን ከፍተኛ ነጥብ (ማርክ) ሰጥቸዋለሁ። የኛን ተጠናክሮ መውጣት አልቻልንም ማለቱ ልክ ነው። አንባቢዎቼ ታስታውሱ ከሆነ እኔ “ኢትዮፓትርዮስትስ” በተባለው የኢትዮጵያ አንድነት ራዲዮ ሲውድን አገር የሚገኘው ድረገጽ ባደረግኩት ቃለ መጠይቅ ላይ “ተቃዋሚው መፍትሔ ፍለጋውን እየጠበቀ ያለው ከወያኔ እና አጋር ድርጅቶቹ ከሚያደርጉት የጥገና ለውጥ ብቻ ታጥሮ መወሰኑ የሚያሳየን የተቃዋሚው “ክራይስስ” (ክስረት) እንደሆነ መግልጼን ያደመጣችሁኝ ታስታውሳላችሁ። ልክ እኔ ያልኩትም ልደቱ አያሌው አጠናክሮልኛል። ጥሩ መልስ ነበር የሰጠው።

ልደቱ ያለው ምንድ ነው? ከአንድ አድማጭ የቀረበው “ተቃዋሚዎች ከኢህዴጎች የድርድር ጥሪ ተድሮጋለችሁ ያውቃል ወይ?” ለሚለው ጥያቄ ልደቱ ሲመልስ “ለድርድር የጋበዘን አካል የለም፡ እየተካሄደ ነው ከሚባለውም ከድርድሩ እንድንወጣ ነው እየተደረግን ያለነው”…ካለ በላ << “ለመሠረታዊው ጥያቄ መልስ ለመስጠት አልቻልንም። ምክንያቱም  “ተቃዋሚው” መፍትሔ እየፈለገ ያለው ከገዢው ፓርቲ ነው። እውነት ነው ሥልጣን የያዘው ገዢ ፓርቲ አገሪቱ በስሩ ስለሆነች ዋናው መፍትሔ ከእርሱ ይጠበቃል።ግን ከሱ ብቻ አይደለም፤ ከኛም ይጠበቃል።>> ብሏል። ይኼ ልክ ነው።

ከልደቱ ጋር ተመሳሳይ መልስ ያስደመጠን ዶ/ር መረራ ጉዲና ነው።

 “መረራ” አጭር እና ጥሩ መልስ ሰጥቷል።“ተቃዋሚዎች ከኢህዴጎች የድርድር ጥሪ ተድሮጋለችሁ ያውቃል ወይ?” ለሚለው ጥያቄ፤ <<ተቃዋሚው ወያኔን በምንም መልኩ ለድርድር ማቅረብ መቻል አለብን>>  ብሏል። ሆኖም እንዴት ለድርደር ማቅረብ አለብን ለሚለው ግን “የተነሳው ሕዝባዊ ቁጣ” ማበረታታት እንዳለባቸው መረራ ቢገልጽም የሕዝቡን ቁጣ ተቃዋሚዎች እንዴት ይምሩት የሚለው (እኔ የቪ ኦ ኤ ጋዜጠኛ ብሆን ያነን ነበር የማቀርብላቸው) መረራም ሆነ ሌሎቹ የሰጡት ፍንጭ የለም፡ አልሰማሁም። ማንኛቸውንም መልስ የላቸውም።

የልደቱ ሌለው ነጥብ ተቃዋሚዎች ወጥ የሆነ ሥርዓቱን የምንገልጽበት መገለጫ እና መፍትሔዎቹ መስማማት ያለመቻላችን ለችግሩ አስተዋጽኦ አድርገናል፡የሚለው ትችቱ ፤ስንመለከት ደግሞ፤ ልደቱ እራሱ ሥርዓቱን የሚገልጽበት መገለጫ ከተቃዋሚዎቹ ጋር የሚያቀራርበው ስላልሆነ መጀመሪያ ልደቱ ሥርዓቱን የሚገልጽበት መገለጫ መነጽሩ ካላስተካከለ ወደ አንድ ወጥ ማግባቢያ የትግል አቅጣጫ ሊመራ የሚችል መስመር አይደልም እራሱ እያካሄደው ያለው ትግል። የልደቱ መጥፎ መስመር ካሁን በፊት ለአንባቢዎቼ ገልጫለሁ።ግልጽ ላደርገው፡ የልደቱ  አያሌው መስመር ምንድ ነው? ካሁን በፊት እንዲህ ሲል የገለጸውን ላስታውሳችሁ

የልደቱ አያሌው መስመር፤ በአንደበቱ እንዲህ ይላል፦

<<“ተቃዋሚዎች ለኢሕአዴግ ያላቸው የተሳሳተ አመለካከት ነው። ከሽግግሩ መንግሥት ጀምሮ የተከተሉትን አስተሳሰብ እስካሁን ድረስ ሊቀይሩት አልቻሉም። ኢሕአዴግ ይህን ሁሉ ልማት እየሰራ፤ ኢሕአዴግ እዚህ አገር የመጣው ‘አገር ለማፍረስ ነው! ለማጥፋት ነው!’ ብሎ እንደ አንድ ውጫዊ ሃይል መፈረጅ ይሄ አብሮ ለመስራት፤ለመመካከር፤አብሮ ለመስራት ትልቅ እንቅፋት የሆነው ይህ አቁዋማቸው ነው። ይህንን እምነታቸው መለወጥ አልቻሉም…..” >>፡ይላል፤ ልደቱ አያሌው ተቃዋሚ የሚባሉት እና ተማሩ የሚባሉ ክፍሎች ከገዢው ፓርቲ ጋር የአዳራሽ የውይይት ስብሰባ ላይ ከተናገረው የተወሰደ።

ልደቱ አያሌው እንዲህ ያለ ወያኔን የሚገልጽበት አቁዋሙ ከሌሎቹ የሚለይ ከሆነ ‘ልደቱ’ <<ይህ መንግሥት አገር ለማፍረስ የመጣ ወራሪ ሃይል ነው>> ብለው ከሚሉት ጋር የተቃራኒ መስመር አለኝ የሚለን ልደቱ አያሌው ዛሬ “ቪኦኤ“ ላይ ቀርቦ << ከመንግሥት በኩል ለድርደር የጋበዘን የለም፡ እንዳውም ድርጅታችን ለማፍረስ እየሞከረ ስለሆነ፤ ፍርድ ቤት ላይ ነን ያለነው፤ ከድረድሩ ተገፍተን ሳንወድ እንድንወጣ ተደርገናል”>> ይላል። ተቃዋሚዎቹ ከልደቱ የተለየ መስመር ስላላቸው “ገዢው መንግሥት ለድርድር ጋብዞ ኣብሮአቸው እንዲሰራ፤እንዲደራደር መንገድ የዘጋው “አገር ሊያፈርስ የመጣ  ወራሪ ሃይል ነው” ስላሉ ነው ካለ፤ “ታዲያ ለምንድነው ይህ ሥርዓት አገር አፍራሽ አይደለም፤ወራሪ አይደለም!” ሲል ተከራካሪ የሆነው ልደቱ አያሌው ከድርድሩ ተገፍትሮ መውጣት ብቻ ሳይሆን የልደቱ ፓርቲ የድርጅቱ (ኢዴአፓ) ህልውና አደጋ ለይ ወድቆ ገዢውን መንግሥት ፍርድ ቤት እንዲሞግት ህልውናውን እስከ መጥፋት እና አብሮ መስራት ያልቻለበት ምክንያት ምንድነው?

ሥርዓቱ ለድርደር ዝግጁ እንዳይሆን የልደቱን ዓይነት መስመር ተቃዋሚው ባለማራመዱ እንቅፋት ሆኗል የሚል ክስ በተቃዋሚ ድርጅቶች ላይ ክስ ካስተጋባ የልደቱን ድርጅት ተደራዳሪዎች ለምን “ድረድር” ከሚባለው ተገፍተው እንዲወጡና በሌሎች አንዲተኩ ተደረገ? የሚለው ልደቱ መልስ ሊሰጠኝ ይገባዋል። እንደውም ለዚህ ሁሉ ችግር መድረስ ተቃዋሚው “በሙሉ” ሥርዓቱን በትከክል የሚገልጸውን “አገር ለማፍረስ የመጣ የወራረዎችን ተልዕኮ ተግባራዊ ለማድረግ ወደ ሥልጣን የመጣ አፍራሽ ሃይል” ነው የሚለው መስመር ይዘው አገር ለሚያፈርስ የመጣን ቡድንም ሆነ መንግሥት ለመመከት የሚደረገው አገር አቀፍ የክተት ሥራ ያልመስራታቸው ለዚህ ሁሉ ችግር ተጋርጠናል። ልደቱ ለዚህ ብልሽት ይህ ነው የማይባል ከፍተኛ ብልሽት በትግሉ ውስጥ ውሃ ከከለሱበት አንዱ ልደቱ ነው።  ሆኖም ልደቱ <<“እኛ እንደ ተቃዋሚዎች ጥርት ያለ አቀውዋም ለሕዝቡ ማስያዝ አልቻልንም”>> በሚለው ላይ ከኔ ጋር ስለሚስማማ ትክክለኛ ተኩስ ተኩሷል።

ሌላው የቪኦኤ” እንግዳ ሆኖ ያደመጥነው፤ ሁላችሁም የምታውቁት “እየተነፋ እንደሚተነፍስ ጎማ ዓይነት ባሕሪ ያለው መያዣ መጨበጫ የሌለው አቁዋመ ቢስ “ሂፒክሪቱ” ብርሃኑ ነጋ መልስ አጥቶ ወዲያ ወዲህ ሲዋዥቅ አገር ለማዳን “ሠላማዊ የሽግግር መንግሥትስ እንዲመሠረት ምን ዓይነት እንቅስቃሴስ እያደረጋችሁ ነው? ተበሎ ለተጠየቀው ጥያቄ መልሱ እንዲህ ይላል-

<<ባንድ በኩል ብዙ ደም ሊያፋስስ ወደ እሚችል አቅጣጫ አገሪቱ አንደምትሄድ እና በሌላ በኩል ወደ ተረጋጋ ለውጥ ሊኬድ የሚችልበት ሁኔታ ሊኖር እንደሚችል እናውቃለን….”>>

ካለ በላ ይቀጥልና

<<“ሶ/so/ ማናችንም አገሪቱ ወደ በየትኛው መንገድ ትሄዳለች የሚለውን ነገር አናውቀውም። ይህ እውቀት ያለው ‘ወታደሩን፤ደህንንቱን’ የሚቆጣጠረው ሃይል ጋር ነው።”>>

ይልና እንደገና

<<‘ያ ሃይል ወዴት እንደሚወስደን ባላወቅንበት ሁኔታ፤በዚህ መልክ ሊኬድ ይችላል፤በዚህ መንገድ መሄድ ይቻላል፤ እያልን በተረጋጋ መንፈስ እንኳ እሰኪ “እንዴት እንሂድበት” ወደ እምትልበት ውይይት መሄድ አትችልም”።>>  
በማለት አገሪቱ ወዴት እያመራች እንዳለች ባላወቅንበት ሁኔታ ለሽግግር መንግሥት የሚያመቻቹ ነገሮች የምንሰራበት እንቅስቃሴ ምንም ምክንያት የለምሲል የሽግግር መንግሥት የሚጠይቀው እንቅስቃሴዎች እንዳላደረገና ለማድረግም ፍላጎት እንደሌለው፤ለዚህም አገሪቱ ወዴት አንደምትሄድ ባላወቅንበት ሁኔታ እንዲህ ያለ እንቅስቃሴ አናደርግም ይላል። ይህ የሚያሳየን፤ ብርሃኑ እና ድርጅቱ ያገሪቱ ፖለቲካ ወደ መፍረስ እየሄደች ስለሆነ “ምን አለፋን” አይነት ደንቆሮ ፖለቲካ እየተከተለ ነው ወይንም ብዙዎቻችን እንደምንለው አምነት የማይጣልበት አታላይ ድርጅትና የሚጎነጉነው ሴራ እንዳለ ፍንጭ መሆኑን ያሳያል። እራሱን በለመደው መደበቅ ሲያምረው እንጂ ከነ ሌልጮ ጋር ምን እያደረገ እንደሆነ፤ በትግሬዎች ስም የሚነግደው የሻዕቢያው የፍተሻ ቡድን “ድምህት” ጋር ግምባር ፈጥሮ ምን እያደረገ እንዳለ፤ ቪዥን ኢትዮጵያ ከተባለው ጋር ምን እያደረገ እንዳለ እናውቃለን። አደልም እንዴ? ሆኖም ንግገሩን እንከተል እና እንተቸው።

ብርሃኑ የሽግግር መንግሥት ምሥረታ እንቅስቃሴ ሊያደርግ የሚችለው የሚከተለው ሁኔታ መደረጉ ማስያዣ (ኢንሹራንስ/መተማመኛ) ሲያገኝ ብቻ ነው። ያ መተማመኛ ደግሞ ከማን ነው የሚያገኘው? ወደ አንደበቱ ልውሰዳችሁ፤

እንዲህ ይላል፦

 <<..ስለዚህ በመጀመሪያ መሆን ያለበት ይሄ ሥርዓት በጉልበትም ሊሄድ እንደማይችል  አውቆ ካሁን በላ እዚህ ድርጅት ውስጥ በተለይ ህወሓት ውስጥ አሁንም በጉልበት እንሄዳለን ሥልጣናችንን ማስመለስ እንችላለን ቢሉ በፍፁም ለነሱም ላገሪቱም አደጋ እንደሆነና እዛ ሥልጣን ላይ ተመልሰው ልይዙ እንደማይችሉ ካወቁ ያንን እንደሚመለከት ደግሞ ግልጽ የሆነ አቅጣጫ ካስቀመጡ “then/ዜን” ያኔ እንዴት ያለ ብሔራዊ መግባባት እና ወደ እውነተኛ የሽግግረ ሂደት የምንገባበት ሁኔታ መኖሩ ከታወቀ፤ያኔ ሁሉም በተረጋጋ መንፈስ ያኔ እንዴት እንሂድበት ብለን መቀጠል ይቻላል። >>  ይላል ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ። አስቂኝም፤ አስቆጪም ፤ፈገግ የሚያሰኝም የብርሃኑ እውነተኛ ስዕል የምናይበት ሌላው አጋጣሚ ነው።

በጣም ይገርማል! <<‘ያ ሃይል ወዴት እንደሚወስደን ባላወቅንበት ሁኔታ፤በዚህ መልክ ሊኬድ ይችላል፤በዚህ መንገድ መሄድ ይቻላል፤ እያልን በተረጋጋ መንፈስ እንኳ እሰኪ “እንዴት እንሂድበት” ወደ እምትልበት ውይይት መሄድ አትችልም”።>> 
በማለት አገሪቱ ወዴት እያመራች እንደለች ባላወቅንበት ሁኔታ ለሽግግር መንግሥት የሚያመቻቹ ነገሮች የምንሰራበት እንቅስቃሴ ምንም ምክንያት የለም ሲለን ወያኔዎች ለብርሃኑ ነጋ (ለግንቦት 7) ግልጽ የሆነ አቅጣጫ ካስቀመጡለት ያኔ “የቪ ኦ ኤው” ጠያቂ የጠየቀው <<“ሠላማዊ የሽግግር መንግሥት እንዲመሠረት ምን ዓይነት እንቅስቃሴስ እያደረጋችሁ ነው? >> ለሚለው ጥያቄ የምንሄድበት መንገድ በዚህ በዚህ ነው ብለን እንቅስቃሴ እንጀምራለን። ይላል። የብርሃኑ የሁሉም ጊዜ ‘ሂፖክሪቲክ” መልሱ “ልክ አንደ “ኢሳያስ አፈወርቂ” ከወዲያ ወዲህ እየጠማዘዘ አድማጮችን ግልጽ መልስ ላለመስጠት የሚጫወተው ጨዋታ “deceitful-lying and dishonesty” የማታለያና የውሸት መልሶች ሁሌም በነዚህ ሁለት ሰዎች ያየቸው ካራክተሮች ናቸው። ባንድ በኩል ‘አገሪቷ’ አስጊ ጎዳና ላይ እና ወደ ደም መፋሰስ ልትሄድ እንደምትችል ያምናል። ባንድ በኩል ወያኔዎች “ግልጽ የሆነ ብርት የማስቀመጥ ፍላጎት ካሳዩ” ሰላማዊ ሽግግር እንደሚደረግ ያትታል።” አንደገና ያንን የተለያዩ መላምቶች ያስቀምጥና ሁኔታው /አገሪቱ/ ወዴት እንደሚታመራ አይታወቅም ይላል። ከወያኔ ግልጽ አቅጣጫ ከመጠበቅ ይልቅ፡ እውነተኛ የፖለቲካ ሰው ሊናገረው የሚገባ ነገር <“ እንደ መስቀል ዳሜራ አገሪቷ የምትወድቅበት አቅጣጫ ማወቅ ካስቸገረው”> ለበጎም ለደግም “ሠርገኛ መጣ በርበሬ ቀንጥሱ” ብሎ ውዥምብር ውስ  ከመግባት የፖለቲካ ድርጅቶች ሃለፊነት ድንገት “ክፍተት” ሲፈጠርም ሆነ ድንገት “ጤነኛ ሽግግርና ድርድር” የሚጋብዝ ሁኔታ ነገ ቢፈጠር “በእጅ ላይ ያለውን ሠላማዊ የሽግግር መንግሥት አቀራረጽ እንቅስቃሴና የያንዳንዱ ድርጅቶች አምነት፤ መንግሥታዊ አወቃቀርና አስተዳዳር፤ ዕርቅ፤ የወንጀል ቅጣት፤ የግዛት አንድነት፤ ውጥንቅጡ ከወጣው የሰንደቃላማ ጉዳይ፤ አሁን የተያዙት የየክልሉ በየነገዶቹ የተሸነሸኑ መልክኣ ምድሮች አቀያየስ፤ የባሕር ወደብ፤ ሉዓላዊነት” ወዘተ የመሳሰሉትን አጀንዳዎች በግልጽ ይዞ መግባት ነው የሚቀለው ፤ ወይስ “ያኔ እናስብበታለን ነው? የሚባለው? ያውም የጠቀስኩዋቸው ነገሮች ያኔ ለወደፊቱ ሳይሆን “ሞረሽ ወገኔ” የተባለው አማራዊ ሲቪክ ማሕበር ከጥቂት ወራት በፊት አቁዋሙን ምን፤ምን መደረግ እንዳለት፤ ምን እንደሚፈልግ ለሕዝብ ይፋ እንዳደረገው ሁሉ ሌሎችም ዛሬውኑ አጀንዳችሁ ነግራችሁን ዜጎች የሚበጀውን የሚጎዳውን የሚጨምርም የሚቀነስም፤ የሚታረምም ካለ ይፋ ማድረግ ይጠበቅባችል። (The oppositions must be aware of their goals and positions and must identify the concerns to the public.. All opposiyions must determine their goals, anticipate what they want to achieve, and prepare for the negotiation process!)

ለነገሩ ሆኖ እንጂ ብርሃኑ ነጋ የሥልጣን ጥም የለኝም፤ግንቦት 7 ለሥልጣን አይታገልም፤ ይበል አይበል፤ እኩልነት ፤ ዲሞክራሲ፤ ሕዝብ ምናምን የሚለው የተለመደው የማታለያ ኮተቱ ለምናውቀው ሁሉ የማታለያ ዘዴ ከመሆን አያልፍም። ብርሃኑነን ለበርካታ አመታት የተከታተልን የፖለቲካ ተቺዎች ብርሃኑን በየመድረኩ ሲናገር በድምጹ የቀዳነውና እየታገለለት ያለው የምናውቀው መስመሩ እናውቀዋለን። ”ማንም ሕዝብ ልገንጠል ካለም ‘አትገነጠልም’ አንለውም፤ መገንጠል ከፈለገ “በሕዝብ ደምፅ” መገንጠል ይችላል”>> ሲል አድምጠነዋል። ብርሃኑ ወይንም ግንቦት 7 እያለን ያለው ማንም አካባቢ የወያኔን አንቀጽ 39 ተጠቅሞ እገነጠላለሁ ካለ ያንን የመገንጠል መብቱ በ51% ተጠቅሞ መገንጠል አንጂ “አገር አታፈርስም” ብለን በጠምንጃ አንይዘውም ሲል ሁሉም የመበታተን መብቱ በሕዝብ ድምጽ እንደሚያስከበር ብዙ ጊዜ ነግሮናል።ለዚህም ነው ከነ ሌንጮ ጋር እየተሻሸ ሰንደቃላማ ሲሰደብም አፉን ዘግቶ በየአዳራሹ ከነ ሌንጮ ጋር ሲሞዳሞድ የምናየው (የጋር መድርክም አላቸው! ይህንን ታውቃላችሁ አደለም?) ያንን “በሕዝብ” እና “በሕዝብ ብቻ” የሚለው ማጃጃያ መስመሩም ዛሬም በቪኦኤ አማርኛ ክፍል ፌስ ቡክ በተዘጋጀው በነ ሄኖክ ሰማ እግዚሔርና ከነ አሉላ ከበደ እንዲሁም ከአድማጮች ጋር በቀረበለት ጥያቄ ሁሉ ያንን “በሕዝብ የሚወሰን ሁሉ እንቀበላለን” መስመሩ ደጋግሞ አስደምጦናል።

የሕዝበ ውሳኔ የሚለው አገር ለማፍረስ የተላኩ ቅጥረኞች የሚጠቀሙባት ጣፋጭ ቃል። ብርሃኑ ነጋ አሜሪካን አገር እየኖረ፤ አሜሪካ አንድም ተገንጣይ ካሜሪካ ግዛት በሕዝብ ድምፅ አስረግጬ ልገንጠል የሚል ጠያቂ ሲኖር ምን መልስ እንደሚነገረው እያወቀ፤ ኢትዮጵያን የምታክል ጥንታዊት አገር “በሕዝብ ድምፅ” እናፈርሳለን እየተባለ ማንኛውንም አገር በድምጽ የተገነባ ይመስል የሥልጣኔና የዲሞክራሲ መገለጫ ነው በሚል “ኢትዮጵያን” በሕዝብ ድምጽ ለማፍረስ ዝግጁ ነኝ በማለት “የሕዝብ ውሳኔ” የሚለው ያረጀ ያፈጀ የሌኒኒስቶች “በሕዘብ ድምፅ ተንተርሶ እስከ መገንጠል” የንህሊስቶች አጀንዳ አሁንም ብዙ የዋህ “ገገማዎችን” የሚያሞኝ ሐረግ በመምዘዝ አገር ለማፍረስ ተዘጋጅቷዋል።

ኢንዲህ ያለ የተጭበረበረ ፖለቲካዊ ሰበካ የመያዙ አጀንዳ በብርሃኑ ነጋ ብቻ ሳይሆን በምክትሉ በንአምን ዘለቀም ኢሳት በተባለ ኔትወርክ የተዘጋጀው ቪዥን ኢትዮጵያ የተባለ በጌታቸው በጋሻው (ዶ/ር ዜሮ) የሚመራው “አፍቃሬ ኦነግ” ጋር በመተባበር በተዘጋጀው መድረክ (ክፍል 3 ቪዲዮ በ2016 በፈረንጅ አቆጣጠር ( ESAT Special Program Vision Ethiopia & ESAT Conference Part 3 ) ሌንጮ ባቲ (የአውሮጳ ብርድ አልቻልኩትም አገሬ ልገባ ነው ያለንን ሽማግሌው ሌንጮ ለታ አይደለም እያልኩ ያለሁት። የአንድነት አስመሳይ ቀኝ አክራሪው ተገንጣዩ ወጣቱ ሌንጮ ባቲን ነው) አዲስ ቀለም ተቀብቶ የመጣብን “ዞር አሉ አልሸሹም” ሌላው የኦነግ ድርጅት ወክሎ ኦሮሞ በሚኒሊክ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ የተቀላቀለች “በኮሊኒ” የተያዘች ነች (እራሱ ከተናገረው ቃል ልድገም እና የጋላ አገር እኮ መቸ እንደተያዘ ሲነገረን በወላጆቻችን ሲነገረን ያደግን ነን) ብሎ እዛው አዳራሽ ውስጥ ጅሎችን ሲያንጨጭብ ከነበረው ከባሌዎቹ  ”አክራሪው” ኦሮሞ ከ“ሌንጮ ባቲ” ጎን ቁጭ ብሎ ንአመን ዘለቀ የተናገረውን ቃል በቃል ላስታውሳችሁ እፈልጋለሁ።

 

ንአምን ዘለቀ እንዲህ ይላል፡

<< The most democtic system, powerful system ችግሮችን ልንፈታ የምንችልበት ሲስተም ዲሞክራቲክ ሲሰተም ነው። እነዚህ ሁለት የሆኑ ፒላሮች የኢትዮጵያ አንድነት እና ዲሞክራሲን ከተቀበልን እኛ ፖሊሲ አንመረምርም! ፖሊሲ የለንም እኛ።ንቅናቄ ነን። የኢትዮጵያ ፖሊሲ ምን ይሁን ፤ማሕበራዊ ፖሊሲ ምን ይሁን፤ ክልላዊ አወቃቀር ምን ዓይነት ይሁን..፤ ምን ዓይነት ፌደራላዊ አወቀቀር ይሁን የሚለው እኛ የለንም። በዚህ ከተስማማመን ወያኔ መወገድ ካለብት ከተስማማን ኩሉም ሃይሎች ጋር መተባበር እንደምንፈልግና አብርን መስራት እንደምንችል ግልጽ አድርገናል።>>  ይላል። (ንአምን ዘለቀ ቪዥን ኢትዮጵያ ከተባለው ‘የካባሎች’ ኔት ወርክ መድርክ ከተናገራቸው የተወሰደ)።   


እዚህ ላይ መሰመር ያለበት ነገር << መተባበር እና አብረን መስራት የምንችለው “የኢትዮጵያ አንድነት” እና  ‘ዲሞክራሲን’ መቀበል እንደ “ቅድመ ሁኔታ” አስቀምጧል። አንድነትን እንደ ቅድመ ሁኔታ እያስቀመጠ፤ አንደንትን የሚያፈርስ “የተለያዩ በዲሞክራሲ ውስጥ የተካተቱ የገሙ የገለሙ ፌደራሊዝም አወቃቀሮችን (ኤትኒክ…ግሩፕ..ፌደራሊዝም..) ያካተተ ዲሞክራሲ (እስከ መገንጠል ሁሉ ዲሞክራሲ ነውና) ነውና እንቀበላለን ይላል።

ቅድመ ሁኔታ ደግሞ፤ <ምን ዓይነት ዲሞክራሲ”? ለሚለው ጥያቄ ሲመልስ “ድፍን ያለ” አሳሳች ዲሞክራሲ እንደሆነ ይነግረናል። ይሄውም ግልጽ ላድርገውና <<ፌዴራላዊ፤ክልላዊ አወቃቀር ምን ዓይነት ይሁን፤ ምንስ ዓይነት ፌደራላዊ አወቀቀር ይሁን የሚለው እኛ የለንም።>> በማለት ያ ለግንጠላ ሃይሎች መንገድ የሚፈቅድ /“ኤትኒክ ፌደራሊዝም”’\ ‘ያውም የወያኔው ዓይነት እና እነ ሌንጮ ባቲ ዓይነት የሚሰብኩትን ‘አሁን ያለው አወቃቀር’ እንዳውም ወደ ክልል ወርዶ “ቡድናዊ መብትን” በማጠናከር ኦቶኖሚውን ለጥጦ ‘እስከ መገንጠል ድረስ’ መፍቀድ የሚችለውን ፌደራሊዝምን የተቀበለ ቡድን ነው። ለዚህ ነው ፤ይህ ድርጅት “ካባል’ ነው ምስጢሩ አደገኛ እና ድብቅ ው የምላችሁ።

ብቻ ወያኔ እንጣል እንጂ ሲወድቅ ያኔ እንደርስበታለን የሚለው አነጋጋር ያኔም ችግር ከሚፈጥሩ አንዱ ግንቦት 7 እንደሆነ የታወቀ ነው። ምክንያቱም ተገንጣዮች አጀንዳቸው አሁን እና ከ40 አመት በፊትም ሠርተውበት አዘጋጅተው፤ተዘጋጅተውበት፤ ሙተውበት፤ ታስረውበት፤ ባንዴራ አቁመውበት፤ ቋንቋ ፈጥረውለት፤ ኦሮሚያ የሚባል አዲስ ክልል ፈጥረው 3/4ኛ መሬት ነጥቀው፤ ሕዝብ አደራጅተው፤ አወናብደውና አንቅተው ወዴት እንደሚሄዱ ስለሚያውቁ፤ እነ ብርሃኑና ንአምን ዘለቀ ግን ለሕዝባችን እየነገሩት ያሉት “ወዴት እንደምትሄድ ላ አንተ የምታውቀው ራስህ ነህ ፤ እዛ ላይ አናቅልህም! እያሉ ያሉትን ገበሬ ለተገንጣዮች እና አክራሪ ቡድኖች አመቻችተው ለጅብ ለመስጠት ተዘጋጅተዋል ማለት ነው።

በመሰረቱ እነ ንአምን (ግንቦት7) የሚሰብኩት “ብቸኛ አማራጭ” The most democtic system, powerful system የሚሉት “ዲሞክራሲ <<“ብዙሃን ይመውኡ”> ማጆርቲ ዊን”“ማጆሪቲ ኦቨር ማይኖሪቲ”ብዙሃኑ በጥቂቶች ህይወት ላይ የመወሰን መብት ያለው”፤  የግለሰብ መብት የሚነጥቅ ስርዓት’ አይደለም ወይ እነ ንአምን “ብቸኛ እና የሰው ልጆች መብት አክባሪ” ብለው በትግሉ ለመተባባር “እንደ ቅድመ ሁኔታ” ያስቀመጡት ዲሞክራሲ የሚሉት?    

አንባቢዎቼ እዚህ ላይ እንድታውቁት የምፈልገው ኢትዮጵያ ሁለት አደገኛ ወጥመዶች ይጠብቋታል። አንደኛው ወጥመድ የወያኔ ወጥመድ ነው። ይኼውም አንደኛው እግርዋን አነጣጥሮ ለመቀርቀብ አፉን ከፍቶ ለመጨረሻ ግብአትዋ ተዘጋጅቶ እየጠበቃት ነው”>>፡ ሌላኛው ወጥመድ <<በዲሞክራሲ ሽፋን ስም በሕዝብ ድምፅ ‘ግንጣለን’ ለማከናወን የተዘጋጀው በነ ብርሃኑ ነጋና በተገንጣይ ሃይሎች የተጠመደው ወጥመድ ነው>>። እነዚህ ሁለት አፍራሾች ፊት ለፊት ቆመው የአገሪቷን እግሮች እንደ ‘ታራጅ ላም’ ጎትተው በመጣል የመጨረሻ ግብአትዋን ለማገባደድ የተዘጋጁ ሁለት ወጥመዶች እንዳሉ ልብ እንድትሉዋቸው እጠቁማለሁ።
አመሰግናለሁ
ጌታቸው ረዳ (ኢትዮጵያን ሰማይ አዘጋጅ)   



No comments: